|
የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ባህልና ቱሪዝም ቢሮ ኃላፊ መልዕክት |
 የአገራችንን ህብረ ብሄሮች ከወግ ፣ልማድና ባህላዊ እሴቶቻቸው ጋር በፍቅር አስተሳስራ ለ125 ዓመት የዘለቀችው አዲስ አበባችን ሌላኛዋ የኢትዮጵያ ማሳያ “ትንሻD ኢትዮጵያ” የሚል ስያሜ ያሰጧትን ጥንታዊ አብያተ ክርስቲያናት ፣ መስጅዶች ፣ ታሪካዊ ቤቶች ፣ ሐውልቶች ፣ሙዚየሞች ፣ ቴአትርና ሲኒማ ቤቶች ፣ ፓርኮችን እንዲሁም የነዋሪዎቿን ባህላዊ እሴቶች በጉያዋ አቅፋ የያዘች እንደመሆኗ መጠን ይህን እምቅ የቱሪስት መስህብ ተጠቅሞ ከተማችንን ብሎም አገራችንን በከፍተኛ ሁኔታ የማስተዋወቅ ድርሻ የዚህ ትውልድ ነው፡፡ ከተማዋ የአገራችን ርዕሰ መዲናና የአፍሪካ ህብረትን የመሳሰሉ ዓለም አቀፍ ድርጅቶች መቀመጫ ከመሆኗ ባሻገር የመስቀል ደመራ ፣ የኢድ ሶላት ፣ የጥምቀት በዓልና ሌሎች ሃይማኖታዊ ስርዓቶች በይፋ የሚከወንባት አውድ ናት፡፡ የአዲስ አበባ ባህልና ቱሪዝም ቢሮም የከተማዋን ባህላዊ ፣ ተፈጥሮአዊና ታሪካዊ ሀብቶች የሚያለማ ፣ የሚንከባከብና የሚጎበኝ ህብረተሰብ የመፍጠር ራዕይ አንግቦ የተቋቋመ ነው፡፡ እንደ አዲስ ፈርሳ እየተገነባች ያለችው አዲስ አበባ ከጊዜ ወደ ጊዜ ምቹነቷን ጠብቃ እንዳማረባት እንድትዘልቅና የከተማችንን ብሎም የአገራችንን መፃዒ ለውጥ ከአምስት ዓመቱ የእድገትና ትራንስፎርሜሽን እቅድ ጋር ለማሳለጥ የከተማዋ አስተዳደር ግዙፍ እቅድ ነድፎ ወደ ተግባር ገብቷል፡፡ ከተማዋ ያሳለፈችውን ማህበራዊ ፣ ፖለቲካዊና ኢኮኖሚያዊ ዳራዎች የሚያንፀባርቁ አሻራዎችና አሁን ያለችበትን ተጨባጭ ሁኔታ በተለመዱ የሚዲያ አማራጮች ብቻ ሳይሆን አዳዲስ አሰራሮችንም ተጠቅሞ በከፍተኛ ሁኔታ በማስተዋወቅ ከተማዋ ለነዋሪዎቿ ምቹ ለጎብኚዎቿም ተመራጭ እንድትሆን መትጋት የወቅቱ ሁነኛ ጥያቄ ከመሆንም ባለፈ የከተማችንን ብሎም የአገራችንን መልካም ገጽታ በማስተዋወቁ ረገድ የሚኖረው ፋይዳ ከፍተኛ ነው፡፡ በመሆኑም የጉብኝት ባህላችንን በማሳደግ ታሪካችንን እና አሁን ያለንበትን መሰረታዊ የእድገት ደረጃ ጠንቅቀን በመገንዘብ ለሌላው የማስተዋወቅ ድርሻችንን እንድንወጣ ጥሪዬን አስተላልፋለሁ፡፡ |
|